Wednesday, March 4, 2015

የነዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ



“ሸላሚም እኛ፣ ከሳሽም እኛ! “
አብርሃም ሰለሞን የ25 ዓመት ወጣት ነው፡፡ ያሳደገው ኢሕአዴግ ራሱ (ወይም ዘመነ መንግስቱ) ነው፡፡ በቤተልሄም የመጀመሪያ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት የ IT መምህር ነበር፡፡ በትምህርት ቤቱ መልካም ዝና ነበረው፡፡ በ2006 በአዲስ አበባ ከተማ በተደረገ ውድድር ላይ ይዞ በቀረበው የመምህራን ዳታ ቤዝ እና የመማሪያ ማኑዋል ዝግጅትን አሸናፊ መሆን ከቻሉ ሦስት ወጣቶች አንዱ ለመሆን በቅቷል፡፡ ጥቅምት 16/2007 - በጠቅላይ ሚኒስትሩ ሸላሚነት ሲካሄድ በነበረው የሳይንስና ቴክኖሎጂ ፈጠራዎች የሽልማት ሥነ ስርዓት ላይ ከ9ኛ እስከ 12ኛ ክፍል ያሉ ተማሪዎችን IT ለማስተማር የሚረዳ የዴስክቶፕ ሶፍትዌር እና የሞባይል አፕልኬሽን በማዘጋጀት የሜዳልያ ተሸላሚ ተብሎ ተመዝግቧል፡፡ ይሁን እንጂ የዘንድሮውን የስራውን ውጤት በአካል ተገኝቶ ሰርተፍኬቱንም፣ ሜዳልያውንም መቀበል አልቻለም፤ በእሱ ፈንታ እናቱ በውክልና ተቀብለውታል፡፡ ምክንያቱም እሱ በሽብር ወንጀል ተጠርጥሮ ቂሊንጦ ማቆያ ቤት ይገኛል፡፡
አብርሃምን ስለ አገሪቱ የወደፊት ተስፋ ሰጪ ስራ ሰርተሃል ብሎ በቀኝ እጁ የጨበጠው መንግስት፣ በግራ እጁ ደግሞ ለአገሪቱ የወደፊት ተስፋ አደገኛ አሸባሪ ነህ ይለዋል፡፡
 

 ከግራ ወደቀኝ አብርሃ ደስታ፣ የሺዋስ አሰፋ፣ ዳንኤል ሺበሺ፣ ዘላለም ወርቃገኘሁ፣ ሀብታሙ አያሌው እና አብርሃም ሰለሞን፡፡
“የማይተዋወቁ ግብረ - አበሮች”
በሽብር የሚከሰሱ ሰዎች ከማያውቋቸው ሰዎች ጋር በአንድ መዝገብ (እንደ ግብረ አበር) የሚታሰሩበት አሰራር የተለመደ ሆኗል፡፡ ለዚህ አንዱ ማሳያ የነዘላለም ወርቅአገኘሁ መዝገብ በመባል የሚታወቀው (መዝገብ ቁጥር 166/07) አንዱ ነው፡፡ በዚህ መዝገብ አራት የተለያዩ ፓርቲ አባላት እና ሌሎች 6 ተጠርጣሪዎች ተከስሰዋል፡፡ የመጀመሪያዎቹ 5 ተከሳሾች (ዘላለም ወርቅአገኘሁ፣ሀብታሙ አያሌው፣ ዳንኤል ሺበሺ፣ አብርሃ ደስታ እና የሺዋስ አሰፋ) በፀረ- ሽብርተኝነት አዋጁ አንቀፅ  4 ሲከሰሱ፣ ቀሪዎቹ አምስቱ (ዮናታን ወልዴ፣ አብርሃም ሰለሞን፣ ሰለሞን ግርማ፣ ባህሩ ዳኑ፣ እና ተስፋዬ ተፈራ) በአንቀፅ 7/1 እና 9ኛ ተከሳሽ (ባህሩ ዳጉ) በሌላ ክስ በወንጀለኛ መቅጫው 288/1 መሰረት ከመከላከያ ሰራዊቱ በመኮብለል ተከስሰዋል፡፡ እነዚህ ሰዎች ክሳቸው በአንድ መዝገብ ታጭቀው ቢመጡም ባብዛኛው እርስ በርስ አይተዋወቁም፤ በጋራ የሰሩት ስራም የለም፡፡
በፌስቡክ እንቅስቃሴው በስፋት የሚታወቀው እና የአረና ትግራይ ፓርቲ አመራር አባል የነበረው አብርሃ ደስታ ለምሳሌ የአንድነት ፓርቲ አመራር አባል ከሆነው ሀብታሙ አያሌው በቀር የሌሎቹን ስም እንኳን አብረው ከመከሰሳቸው በፊት አለመስማቱን ይናገራል፡፡ ተሸላሚው አብረሃም ሰለሞንም ከተከሳሾች የሚያውቀው ዘላለምን ብቻ ነው፡፡ ‹‹እሱንም›› ይላል አብርሃም ‹‹በ2006 አንድም ቀን አግኝቼው አላውቅም››፡፡ ከተከሳሾች መካከል ብዙ ሰው ያውቃል የተባለለት 1ኛው ተከሳሽ ዘላለም እንኳን የሚያውቀው ሦስቱን ብቻ ነው - ዮናታን፣ አብርሃምን እና ባሕሩን ብቻ፡፡

“በስልክ የማውራት አሸባሪነት”
በሽብር የተከሰሱ ሰዎች ላይ በተደጋጋሚ እና በተለይ ከሚቀርቡ የማስረጃ ዓይነቶች አንዱ የስልክ ግንኙነት ነው፡፡ ከላይ በጠቀስነው መዝገብ ውስጥ ብቻ ክስ ሆነው የቀረቡትን የስልክ ግንኙነቶች እንመልከት፡-

  • 1ኛ ተከሳሽ ዘላለም ወርቃገኘሁ፣ ‹‹በ 2000 ተድላ ደስታ ከተባለ የሽብር ድርጅቱ አባልና አመራር ጋር በስልክ እና በፌስቡክ›› በማውራት
  • 2ኛ ተከሳሽ ሀብታሙ አያሌው ‹‹ዘመኑ ካሴ ከተባለ የግንቦት ሰባት ታጣቂ›› ጋር በጥር 14/2005 በስልክ በማውራት፤
  •  3ኛ ተከሳሽ ዳንኤል ሺበሺ ‹‹የግንቦት ሰባት አመራር ከሆነው ፋሲል የኔ አለም ›› ጋር በየካቲት 29/2003 በስልክ በማውራት፤
  •  4ኛ ተከሳሽ አብርሃ ደስታ ‹‹የደ.ም.ሕ.ት. አመራር ከሆነው ጎይቶም በርሄ ›› ጋር ጥር 3/2006 በስልክ በማውራት፤ 
  •  5ኛ ተከሳሽ የሺዋስ አሰፋ ‹‹የግንቦት ሰባት አመራር ከሆነው ፋሲል የኔአለም›› ጋር ጥቅምት 14/2006 በስልክ በማውራት፤
  • 10ኛ ተከሳሽ ተስፋዬ ተፈሪ፣ የግንቦት ሰባት ክንፍ ከሆነው የአ.ዴ.ኃ.ን አባል ጋር ሕዳር 2003 በስልክ በማውራት፤

እነዚህ የስልክ ግንኙነቶች ያለሌላ ተጨማሪ ማስረጃ በብቸኝነት የክስ መመስረቻ መሆናቸው ደግሞ ክሱን ተአማኒነት ያሳጡታል፡፡ ዜጎች የስልክ ግኑኝነቶችን በሙሉ እንዲፈሩም ያደርጋቸዋል፡፡ በሽብርተኝነት በተጠረጠሩ ድርጅቶች ውስጥ በዐቃቤ ሕጉ ቃል ብቻ አባል ናቸው የተባሉ ሰዎች ስለደወሉለት ብቻ የተደወለለት ሰው ‹‹አሸባሪ›› ተብሎ ይከሰሳል፡፡ ፈቅዶ ባልተደወለለት ስልክ ወንጀለኛ ነህ የሚባልበት አሰራር ከኢትዮጵያ ውጪ ያለ አይመስልም፡፡ አንዳንዶቹ የስልክ ጥሪዎች የተደረጉት ‹‹ሽብርተኛ ናቸው›› በተባሉ ድርጅቶች ውስጥ ባሉ እና በሚታወቁ ግለሰቦች ሳይሆን የአቃቤ ህግ ቃል ብቻ ያልሆነውን ነው ብሎ ስላቀረበ ነው፡፡ በዚህ መንገድ የተፈረደባቸው ብዙ ናቸው፡፡ ሳይፈረድባቸው ራሳቸውን ለመከላከል ማረሚያ ቤት እንዲቆዩ የተደረጉትም የዚያኑ ያክል ናቸው፡፡ በ2000 የፀረ ሽብርተኝነቱ አዋጅ አልወጣም ነበር፤ ሽብርተኛ የተባሉ ድርጅቶችም አልነበሩም፡፡ ክሱ ላይ ግን በዚያ ወቅት የተደረገ የስልክ ግንኙነት ተጠቅሷል፡፡
በሁሉም የሽብር ክሶች ውስጥ copy/paste የተደረገች ውንጀላ አለች፤ ‹‹ራሱን [እከሌ ]ብሎ ከሚጠራው አሸባሪ ቡድን ግንኙነት በመፍጠርና ተልእኮ በመቀበል ሕገ-መንግስታዊ ስርዓቱን በኃይል ለመናድ በማሰብ . . . ‹‹የምትል ነች፡፡ ይህች ቃል ዐቃቤ ሕግ በተጠርጣሪዎች ላይ ምንም ዓይነት ድርጊት ሳይጠቅስ የሚያስቀጣበት ውንጀላ  ነች፡፡ በዚሁ በነዘላለም መዝገብም ላይ በተደጋጋሚ ተጠቅሳለች፡፡ በስልክ አንድ ሰው ጋር ያወራሉ ከዚያ ተልእኮ ይቀበላሉ፡፡ ሽብር ማለት በቃ ይኽው ነው፡፡

“ሥልጠናዎች ሁሉ ሽብር ናቸው”
በነዘላለም መዝገብ ከተከሰሱት ውስጥ 6ኛ እና 9ኛ ተከሳሽ(ዮናታን እና ባሕሩ) ክስ ላይ የተጠቀሰ ነገር አለ፡፡ይኸውም ‹‹ በመንግስት ላይ ያሉ ችግሮችን ለሕዝብ በተለያዩ የኢንተርኔትና የማህበራዊ ድህረ - ገፆች ላይ በመፃፍ ለግል ሚዲያዎች ግብአት የመስጠት ሥራ የሚሰሩ ቡድኖች አሉ፡፡ ለዚሁ ተግባር ተብሎ የወሰዱትን የኢንተርኔት አጠቃቀም፣ ኮሙኒኬሽን ስኪል እና ሊደርሺፕ በመሰልጠን ተጠቅመዋል እናንተስ እንዲህ አይነት ስልጠና አትፈልጉም ወይ?›› በሚል አንደኛ ተከሳሽ ለሁለቱ ተከሳሾች ቀርበዋል የተባሉት ጥያቄዎች ወንጀል ተብለው ተፅፈዋል፡፡ ‹‹ሠልጥነዋል›› ተብለው በምሳሌው የተጠቀሱት ‹‹ቡድኖች›› ዞን ዘጠኞች መሆናቸው በሌላ ማስረጃ ተጠቅሷል፡፡ሥልጠናውን ዐቃቤ ሕግ 9ኛ ተከሳሽ ላይ ሲጠቅሰው መጀመሪያ ‹‹ተመሳሳይ ሥልጠና ለተመሳሳይ አላማ ›› ይልና ዝቅ ብሎ ‹‹የሽብር ድርጅቱን ተልዕኮ ለመፈፀም እንዲረዳቸው ባዘጋጁት ስልጠና ›› ይላል፡፡ የመንግስታችን ችግሮች መፃፍ ፣ ወይም ለመፃፍ መሰልጠን በምን መሥፈርት አሸባሪነት ተባለ?

“አብርሃም ሰለሞንን ማን መለመለው?”
የክስ መዝገቡ መጀመሪያ ላይ ‹‹[አብርሃም ሰለሞን] በ1ኛ ተከሳሽ  [ዘላለም] አማካኝነት ለሽብር ድርጅቱ በአባልነት ተመልምሎ . . . ›› ይላል፡፡ አንድ አንቀፅ ዝቅ ብሎ ደግሞ ‹‹[አብርሃምን] በአባልነት የመለመለው አንደኛ የአቃቤ ሕግ ምስክር [እዮብ] አማካኝነት . . . ›› ይላል፡፡ አብርሃምን የመለመለው ዘላለም ወይስ እዮብ? (ብቸኛው የዐቃቤ ሕግ ምስክር) መልምሏል የተባለው አብርሃምን ብቻ አይደለም፡፡ 8ተኛ ተከሳሽ ሰለሞን ግርማንም ጭምር እንጂ፡፡ እዮብ ሰለሞንን ሲመለምል ተናግሯል የተባለው ይህንን ነው፤
‹‹ኤርትራ ሀገር ግንቦት ሰባት የተባለ ጥሩ ድርጅት አለ፡፡ ወታደራዊ እና ፖለቲካዊ ሥልጠና ሠልጥነህ ከድርጅቱ ጋር ከተቀላቀልክ በኋላ ግንቦት ሰባት የሚሰጥህን ተልዕኮ ተቀብለህ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር እንዋጋለን፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት ሕዝቡን በኃይል እየገዛ ነው ስለዚህ ታግለን መጣል አለብን፡፡ ››
የዐቃቤ ሕግ ምስክሮች ከተጠርጣሪዎች ጋር ታስረው ቆይተው ኋላ ላይ ምስክር ለመሆን ሲስማሙ መለቀቃቸው የተለመደ ነው፡፡ የፀረ ሽብር ሕጉ ሽብርን ለማጋለጥ ለተባበረ ርሕራሔው ይኼን ይመስላል፡፡ ነገር ግን ክፍተት አለው፡፡ ተጠርጣሪዎች በአባሪዎቻቸው ወይም ሌሎች ላይ መስክረው መፈታት እንደሚችሉ ቃል ሲገባላቸው በሐሰትም ቢሆን ለማድረግ የሚስማሙበት ዕድል አለ፡፡ በዚህ መንገድ መልማዩ ምስክር ሆኖ የሚቀርብበት ተመልማዩ ላይ ይሆናል፡፡
በዚህ ዓይነት መንግስት ያልወደደውን ፖለቲከኛ (ዜጋ) ስልክ ሲደወል ደዋዩ አሸባሪ ነው በማለት፣ ወይም የራሱን ሰው ልኮ በማባበል ለ‹‹ሽብር›› መልምሎ ሲያበቃ መልማዩን ምስክር ተመልማዩን ተከሳሽ ለማድረግ ወይም ደግሞ በስጋት ሰብስቦ ካሰራቸው ሰዎች መሃከል ለነፍሳቸው ግድ የሌላቸው የሃሰት መስካሪዎችን እያሰለጠነ እየፈረደ ሊኖር ይሆን?!  

No comments:

Post a Comment